20/04/2022
የግል ከፍተኛ ትምህርት ተቋማት በአግባቡ አገልግሎት የሚሰጥ ድረ-ገጻቸውን ለባለሥልጣኑ እንዲያሳውቁ ተጠየቀ
====== ========
የኢፌዲሪ ትምህርትና ስልጠና ባለሥልጣን ሁሉም የግል ከፍተኛ ትምህርት ተቋማት በአግባቡ አገልግሎት የሚሰጥ ድረ-ገጻቸውን እንዲያሳውቁ ሚያዝያ 10/2014 ዓ.ም በጻፈው ደብዳቤ አሳሰበ፡፡
ድረ-ገጽ ለማንኛውም የግል ከፍተኛ ትምህርት ተቋም አሠራሩን እና የተቋሙን ሁኔታ ለተማሪዎች እና ለማህበረሰቡ በግልጽ ለማሳወቅ የሚያስችላቸው መሆኑ እየታወቀ አንዳንድ ተቋማት ድረ-ገጽ (Website) የሌላቸው እና በአግባቡ አገልግሎት የማይሰጥ መሆኑን ባደረገው ማጣራት ማረጋገጡን ባለሥልጣኑ ገልጿል፡፡ በመሆኑም ድረ-ገጽ ያላቸው የተቋማቸውን የድረ-ገጽ አድራሻ ለባለስልጣን መስሪያ ቤቱ በደብዳቤ እንዲያሳውቁ ጠይቋል፡፡
እንዲሁም በአግባቡ የማይሰራ ድረ-ገጽ ያላቸው ተቋማት በማስተካከል በተመሣሣይ ሪፖርት እንዲያደርጉ እና ድረ-ገጽ (Website) የሌላቸው ተቋማት ከሚያዝያ 10/2014 ዓ.ም ጀምሮ በአንድ ወር ጊዜ ውስጥ አዘጋጅተው ለአገልግሎት ክፍት በማድረግ ለባለስልጣኑ ሪፖርት ማድረግ እንዳለባቸው አሳውቋል።
እንዲሁም የሁሉም የግል ከፍተኛ ትምህርት ተቋማት የድህረ ገጽ (Website) ዶሜን .edu.et መሆን እንዳለበት እና በባለሥልጣኑ የሚመለከታቸው የስራ ክፍሎች በቀጣይም የእውቅና ፈቃድ እና የእውቅና እድሳት በሚጠየቅበት ወቅት ድረ-ገጽ (Website) አስገዳጅ መስፈርት ሆኖ እንዲገመገም ባለሥልጣን መ/ቤቱ አሳስቧል፡፡ ተቋማት ድረ-ገጻቸውን ሲያሳውቁ ተማሪዎች እና ህብረተሰቡም እንዲያውቁት የሚደረግ ይሆናል።